Tuesday, January 17, 2012

ኢትዮጵያ፡ የግዳጅ ሰፈራ ረሃብ እና ችግር ያስከትላ


***ጉልህ ምስሎችን ለመመልከት http://www.hrwnews.org/press/ethiopia_gambellavillagization.zip ይጎብኙ


የለጋሾች ገንዘብ ተወላጅ ሕዝቦችን ለማንገላታት መዋል የለበትም 
(ለንደን፣ ጥር 9 ቀን 2004 ዓ.ም.) – “ሰፈራ” በመባል በሚታወቀው ፕሮግራሙ የኢትዮጵያ መንግስት 70,000 የሚደርሱ የምዕራባዊ ጋምቤላ ተወላጆችን በግዳጅ በማፈናቀል በቂ የሆነ ምግብ፣ የእርሻ መሬት፣የጤና አገልግሎት እንዲሁም የትምህርት ተቋማት ወደማይገኙባቸው አዳዲስ መንደሮች እንዲሰፍሩ በማድረግ ላይ ነው ሲል ሂዩማን ራይትስ ዎች ዛሬ ባወጣው ሪፖርት ገለጸ። የግዳጅ ሰፈራውን የተቃወሙ የአካባቢው ተወላጆች በመንግስት የጸጥታ ሃይሎች ተደጋጋሚ ማስፈራራት፣ድብደባና ሕገወጥ እስራት ተፈጽሞባቸዋል።


“ ‘ሞትን እዚሁ መጠበቅ’ ፡ የግዳጅ ማፈናቀልና  ‘ሰፈራ’ በኢትዮጵያ የጋምቤላ ክልል” የሚል ርዕስ ያለው ይኸው ሪፖርት የጋምቤላን የሰፈራ ፕሮግራም   የመጀመሪያ ዓመት ሂደት ይፈትሻል። ሪፖርቱ በተጨማሪም የሰፈራ ፕሮግራሙ ያለሰፋሪዎቹ ፈቃድ የሚካሄድ መሆኑን፣ ሰፋሪዎቹን መተዳደሪያና የኑሮ መሠረት ማሳጣቱን፣ እየከፋ የሄደውን የምግብ  (እጥረት) ሁኔታና የኢትዮጵያ የጦር ሃይል በእነዚህ ዜጎች ላይ በመፈጸም ላይ ያለውን ማንገላታት የሚዘረዝር ነው። የሚፈናቀሉት ዜጎች እንዲለቋቸው የሚደረጉት ብዙዎቹ አካባቢዎች መንግስት ለሰፋፊ የንግድ ግብርና ልማት በሊዝ ለማከራየት የመደባቸው ናቸው።
“የኢትዮጵያ መንግስት የሰፈራ ፕሮግራም ለጋምቤላ ተወላጅ ሕዝቦች የሚሰጡ አገልግሎቶችን ተደራሽነት ከማሻሻል ይልቅ የኑሮ መሰረታቸውን እና የምግብ ዋስትናቸውን እያመናመነ ነው” ያሉት የሂዩማን ራይትስ ዎች የአውሮፓ ዳይሬክተር ያን ኢግላንድ መንግስት ተፈላጊ የመሰረተ ልማት አውታሮች መሟላታቸውን፣ ከሚፈናቀሉት ዜጎች ጋር ተገቢ ምክክር መደረጉን እንዲሁም መሬታቸውን ለሚያጡት ወገኖች ተመጣጣኝ ካሣ መከፈሉን እስኪያረጋግጥ ድረስ ፕሮግራሙን ማቆም አለበት።” ብለዋል።
መንግስት የሰፈራ ፕሮግራሙ ለሚሰፍሩት ዜጎች መሠረታዊ የማህበራዊና ኢኮኖሚያዊ መሠረተ ልማት አገልግሎቶችን በማቅረብ ማህበራዊ፣ ኢኮኖሚያዊና ባሕላዊ ለውጥ ለማምጣት የታለመ ነው ይላል። ይሁንና ሂዩማን ራይትስ ዎች እንደሚለው መንግስት
ተመጣጣኝ ካሣ ለመስጠት ቃል ቢገባም የሰጠው ግን ሰፋሪዎቹን በአዳዲሶቹ መንደሮች ለማቋቋም በቂ ያልሆነ ክፍያ ነው።
በአብዛኛው የአኙዋክ እና የኑዌር ጎሳ አባላት የሆኑት የጋምቤላ ተወላጅ ነዋሪዎች ለሚኖሩበትና ለሚጠቀሙበት መሬት መደበኛ የባለቤትነት ማረጋገጫ ሰነድ ኖሯቸው አያውቅም። መንግስትም አዘውትሮ እንደሚለው አካባቢዎቹ “ሰው የማይኖርባቸው” እና “በበቂ ሁኔታ ጥቅም ላይ ያልዋሉ” ናቸው። ይህ የመንግስት አቋም ደግሞ እነዚህ ሕዝቦች ከመኖሪያቸው እንዳይፈናቀሉ ጥበቃ የሚያደርጉትን የሕግና የሕገ መንግስት ድንጋጌዎች እንዲተላለፍ አስችሎታል።
ሪፖርቱ በግንቦት እና ሰኔ 2003  ዓ.ም.  በኢትዮጵያ ውስጥ፣እንዲሁም ብዙ የጋምቤላ ተወላጆች ሸሽተው በተሰደዱባቸው ደዳብ በሚገኘው የስደተኞች ካምፕ እና በናይሮቢ ኬንያ በተደረጉ ከ 100 በላይ ቃለ ምልልሶች ላይ በመመስረት የተዘጋጀ ነው።
ከዚህ ቀደም የአካባቢው ነዋሪ የነበረ አንድ ሰው ለሂዩማን ራይትስ ዎች እንደገለጸው  “አባቴ እንደ ሌሎች የሀገር ሽማግሌዎች ወደ ሌላ አካባቢ መስፈርን ባለመቀበሉ ተደብድቧል።  ‘የተወለድኩት እዚህ ነው፣ልጆቼ የተወለዱት እዚህ ነው፤ ወደ ሌላ ቦታ ሄዶ ለመስፈር ዕድሜዬ ገፍቶአል፤ ስለዚህ እዚሁ እቆያለሁ’ በማለቱ በመከላከያ ሠራዊት አባላት በዱላ እና በሰደፍ ተደብድቦአል። ወደ ሆስፒታል ተወስዶ ነበር፤ነገርግን በድብደባው ምክንያት ሕይወቱ አልፏል።እንዲያው ከጊዜ ወደ ጊዜ እየደከመ ሄዶ ነበር።” 
የሰፈራ ፕሮግራሙ  እ.ኤ.አ. እስከ 2013 ድረስ የኢትዮጵያ መንግስት 1.5 ሚሊዮን የሚሆኑ ዜጎችን በአራት ክልሎች መልሶ ለማስፈር አቅዶአል። እነዚህ ክልሎች ጋምቤላ፣አፋር፣ሶማሌ እና ቤኒሻንጉል ጉሙዝ ናቸው። የሰፈራ ሂደቱ በ 2002 ዓ.ም. በጋምቤላ የተጀመረ ሲሆን እስከ 2004  ዓ.ም. የመጀመሪያ አራት ወራት ድረስ በዚህ ክልል የሚኖሩ 70,000 የሚደርሱ ዜጎችን በሌሎች አካባቢዎች ለማስፈር መርሀ ግብር
ተነድፏል። በጋምቤላ ሕዝቦች ብሔራዊ ክልላዊ መንግስት ዕቅድ መሠረት 45,000 ቤተሰቦች በሦስት ዓመቱ የፕሮግራም ጊዜ ውስጥ በሌሎች አካባቢዎች ይሰፍራሉ። ዕቅዱ ለአዳዲሶቹ መንደሮች የመሠረተልማት አውታሮች እንደሚሟሉና ሰፋሪዎቹም አማራጭ የኑሮ መሠረቶችን እንዲያገኙ እገዛ እንደሚደረግ የሚገልጽ ነው። ዕቅዱ በተጨማሪም እነዚህን ዜጎች ከሚኖሩበት ቦታ አንስቶ ወደሌላ አካባቢ የማስፈሩ ሂደት በፈቃደኝነት የሚከናወን መሆኑን ይገልጻል።ይሁን እንጂ የተሻለ የመንግስት አገልግሎቶች ተደራሽነትን ከማረጋገጥ ይልቅ አብዛኞቹ አዳዲስ መንደሮች እነዚህ አገልግሎቶች ጭራሽ የማይገኙባቸው ናቸው። የመጀመሪያው ዙር በግዳጅ የማስፈር ሂደት የተከናወነው በጣም ተገቢ ባልሆነ ወቅት ማለትም የምርት መሰብሰብ በሚካሄድበት ወቅት ነው። ከዚህም በላይ ሰፋሪዎቹ እንዲሰፍሩባቸው የተደረጉት ብዙዎቹ አካባቢዎች ደረቅና የአፈር ለምነታቸውም ዝቅተኛ የሆኑ ናቸው። በአካባቢዎቹ የሚገኙት መሬቶች መመንጠር የነበረባቸው ሲሆን የዘር እህልና ማዳበሪያን የመሳሰሉ የግብርና ግብአቶች ለሰፋሪዎቹ አልቀረቡም። መንግስት ለሰፋሪዎቹ የምግብ ዕርዳታ ባለማቅረቡም የከፋ ረሃብ ተከስቶአል፤ የምግብ እጥረት ያጋጠመበት ሁኔታም ተስተውሎአል።
የሂዩማን ራይትስ ዎች ጥናት እንዳሳየው ይህ በግዳጅ የማስፈር ፖሊሲ የበርካታ የክልሉ ነዋሪዎችን የሕልውና ሚዛን እያዛባ ነው። በጋምቤላ ክልል ያለው የኑሮና የምግብ ዋስትና ሁኔታ አስተማማኝ አይደለም። አርብቶ አደሮች በከብት ርቢ ላይ የተመሠረተ
ኑሮአቸውን በመተው ሰብል በማምረት ግብርና እንዲሰማሩ እየተገደዱ ነው። የዓመቱን የተለያዩ ወቅቶች በመከተል ከአንድ ቦታ ወደሌላ ቦታ በመዘዋወር ሰብል የሚያመርቱ አርሶ አደሮች በአንድ ቦታ ተወስነው የግብርና ሥራ እንዲሰሩ እየተደረጉ ነው። ይህ ደግሞ የመሬታቸውን የአፈር ለምነት የማሟጠጥ አደጋ ያስከትላል። ሂዩማን ራይትስ ዎች እንደሚለው ትርጉም ያለው የመሠረተልማት አውታሮች ድጋፍና አስተማማኝ የምግብ ዕርዳታ አቅርቦት በሌለበት ሁኔታ የሚደረገው ይህ ለውጥ በአርብቶ አደሮቹም ሆነ በተዘዋዋሪ አርሶ አደሮቹ  ሕይወት ላይ አደጋ የሚጋርጥ ነው።
አንድ ሰፋሪ ለሂዩማን ራይትስ ዎች ሲናገሩ  “መሬቱን በወቅቱ ባለመመንጠራቸው በሚቀጥለው ዓመት የከፋ የምግብ እጥረት እንደሚከሰት እንጠብቃለን። መንግስት መሬቱን መንጥሮ ለእርሻ አዘጋጅቶት ቢሆን ኖሮ ለቀጣዩ ዓመት ምግብ ይኖረን ነበር፤ አሁን ግን ምግብ የምናገኝበት ምንም መንገድ የለም።”ብለዋል። የመሬት ኢንቨስትመንት የሰፈራ ፕሮግራሙ የሚካሄደው ሰፊ የመሬት ኢንቨስትመንት እንዲካሄድባቸው በታቀደ ወይም ኢንቨስትመንቱ እየተካሄደባቸው ባሉ አካባቢዎች ነው። የጋምቤላ ተወላጅ ሕዝቦችን ከሚኖሩባቸው አካባቢዎች በማንሳት ወደ ሌሎች አካባቢዎች የማስፈሩ ተግባር የአካባቢውን ሰፋፊ የእርሻ መሬት ለንግድ ግብርና በሊዝ ከማከራየት ጋር የተያያዘ አይደለም ሲል የኢትዮጵያ መንግስት በተደጋጋሚ ያስተባብላል። ይሁንና የሚፈናቀሉበት መሠረታዊ ምክንያት ይኸው እንደሆነ ነዋሪዎቹ በመንግስት ባለስልጣናት ተነግሯቸዋል። የክልሉ መንግስት የቀድሞ ባለስልጣናትም ይህንኑ ለሂዩማን ራይትስ ዎች አረጋግጠዋል።
አንድ አርሶ አደር ለሂዩማን ራይትስ ዎች እንደገለጹት የመንግስት ተወካዮች ከመንደራቸው ነዋሪዎች ጋር ባደረጉት የመጀመሪያ ስብሰባ ላይ የመንግስት ባለስልጣናት “ለገበያ የሚሆኑ ሰብሎችን የሚያመርቱ ባለሀብቶችን እንጋብዛለን፤ መሬቱን በአግባቡ እየተጠቀማችሁበት አይደለም፤መሬቱ ጾም እያደረ ነው።’’ሲሉ ተናግረዋል ብለዋል።
አንድ አዛውንት ለሂዩማን ራይትስ ዎች ሲናገሩ  “መንግስት እዚህ ያመጣን እዚሁ እንድንሞት እንደሆነ ግልጽ እንዲሆንላችሁ እንፈልጋለን። መንግስት የአኙዋክን ሕዝብ እዚህ እንዲሞት እንዳመጣው ዓለም እንዲሰማ እንፈልጋለን። ምግብ አልሰጡንም፤ መመለስ እንዳንችል መሬታችንን ለውጭ ዜጎች ሰጡብን። በሁሉም አቅጣጫ መሬታችን ተወስዷል፤ ስለዚህ እዚሁ በአንድ ቦታ እንሞታለን።” 
ብለዋል።
ተገቢውን ሕጋዊ ሂደት ሳይከተል ለንግድ ግብርና ሲባል ነዋሪዎችን ከመኖርያ ቦታቸው በጅምላ የማፈናቀል ድርጊት የኢትየጵያን ሕገ መንግስትና የተወላጅ ሕዝቦችን መብቶች የሚመለከተውን ዓለማቀፍ ሕግ የሚጥስ ነው። እ.ኤ.አ. ከ 2008 እስከ ጥር ወር 2011  ባለው ጊዜ ኢትዮጵያ ቢያንስ 3.6 ሚሊዮን ሔክታር መሬት በሊዝ አከራይታለች። ይህም መሬት ስፋቱ ኔዘርላንድስን የሚያክል ነው። ሌላ ተጨማሪ 2.1 ሚሊዮን ሔክታር ለግብርና ኢንቨስትመንት የተዘጋጀ መሬት ደግሞ በፌደራል መንግስቱ የመሬት ባንክ በኩል ይገኛል። የመንግስት መረጃ እንደሚያሳየው በጋምቤላ ክልል 42  በመቶ የሚሆነው የክልሉ መሬት ለባለሀብቶች በሊዝ በመሰጠት ላይ ነው ወይም አስቀድሞ ተሰጥቷል። ነዋሪዎች እንዲለቋቸው የተደረጉት ብዙዎቹ አካባቢዎች በእነዚህ ለግብርና ኢንቨስትመንት በተከለሉ አካባቢዎች ውስጥ የሚገኙ ናቸው። ኢግላንድ እንደሚሉት  “የሰፈራ ፕሮግራሙ የሚካሄደው መንግስት ለሰፋፊ የንግድ ግብርና ሥራዎች ለውጭ ባለሀብቶች በሊዝ እያከራያቸው ባሉት አካባቢዎች ነው። ይህ ደግሞ የሰፈራ ፕሮግራሙ የሚካሄድበት መሠረታዊ ምክንያት ላይ ጥርጣሬን የሚያስነሳ ነው።” 
 የውጭ ለጋሾች ሚና  የኢትዮጵያ ለጋሾች የሆኑት እንግሊዝ፣ዩናይትድ ስቴትስ፣የዓለም ባንክ እና የአውሮፓ ህብረት በሰፈራ ፕሮገራሙ ቀጥተኛ ተሳትፎ የሌላቸው መሆኑን ይገልጻሉ። ይሁን እንጂ በለጋሾች ቡድን የገንዘብ ድጋፍ የሚተገበረው የመሠረታዊ አገልግሎቶች ጥበቃ  (ፒቢኤስ)  በመባል የሚታወቀው ፕሮግራም እንደ ጤና፣ትምህርት፣ግብርና፣የመንገዶች ግንባታ እና የውሃ አቅርቦት ለመሳሰሉት መሠረታዊ
አግልግሎቶች ድጎማ የሚደረግበት ከመሆኑም በላይ በመላ ሀገሪቱ የሚገኙ ወረዳዎች የአካባቢ መንግስታት ሠራተኞች ደመወዝም በዚህ ፕሮግራም የሚደጎም ነው። እነዚህ አካባቢዎች ደግሞ አዳዲስ መንደሮች የሚመሰረቱባቸውን ወረዳዎች የሚጨምሩ ሲሆን
የእነዚህ አከባቢዎች የመንግስት መዋቅሮች ደግሞ ዋና ሥራቸው ነዋሪዎችን ከመኖሪያቸው ማስነሳት ነው።
ሊኖርባቸው የሚችለውን ሃላፊነትና ግዴታ በመገንዘብ ለጋሾች በጋምቤላና በቤኒሻንጉል ጉሙዝ የሚካሄዱትን የሰፈራ ፕሮግራሞች ከገመገሙ በኋላ ነዋሪዎችን ከመኖሪያ አካባቢያቸው ወደ ሌሎች ቦታዎች የማስፈሩ ሂደት በፈቃደኝነት የሚካሔድ ነው የሚል
ድምዳሜ ላይ ደርሰዋል። ሂዩማን ራይትስ ዎች በመስክ በመገኘት ያካሄደው ጥናትና ከነዋሪዎቹ ጋር ያካሄዳቸው ቃለ ምልልሶች የሚያሳዩት ግን ሰፈራው በግዳጅ የሚካሄድ መሆኑን ነው።
ሂዩማን ራይትስ ዎች እንደገለጸው  ዓለማቀፍ ለጋሾች ለግዳጅ ማፈናቀል ድጋፍ እየሰጡ እንዳልሆነ እና በልማት ስም የመብቶችን ጥሰት እያገዙ አለመሆኑን ማረጋገጥ አለባቸው። ለጋሾቹ የኢትዮጵያ መንግስት በኢትዮጵያ እና በዓለማቀፍ ሕግጋት መሠረት ያሉበትን ግዴታዎች ማለትም ስለሰፈራ ሂደቱ ከሰፋሪዎች ጋር ሀቀኛ ምክክር ማድረግን፣ተወላጆችን ከአካባቢያቸው ወደ ሌላ ስፍራ የማስፈሩ ሂደት በፈቃደኝነት እንዲሆን ማድረግን፣ተገቢውን ካሳ መክፈልን፣ በሰፈራ ሂደቱና ከዚያ በኋላም የሚጸሙ የሰብአዊ መብቶች ጥሰቶችን መከላከልን እንዲሁም በጥሰቶቹ የሚሳተፉትን በሕግ እንዲጠየቁ የማድረግን ሃላፊነቶቹን እንዲወጣ ግፊት ማድረግ አለባቸው ብሏል ሂዩማን ራይትስ ዎች። ለጋሾቹ በተጨማሪም መንግስት በአዳዲሶቹ መንደሮች የሚሰፍሩትን ዜጎች ኢኮኖሚያዊና ማህበራዊ መብቶች ለማክበር፣ለመጠበቅ እና ለማሟላት ያሉበትን ግዴታዎች መወጣቱን ማረጋገጥ ይኖርባቸዋል። ኢግላንድ እንደሚሉት  “ለጋሾች የሚሰጡት ገንዘብ ቢያንስ በተዘዋዋሪ መንገድ የሰፈራ ፕሮግራሙን ለማካሄድ እየዋለ ይመስላል። ለጋሾች የሚሰጡት ዕርዳታ የግዳጅ ማፈናቀልንና ተያያዥ የመብት ጥሰቶችን ለመፈጸም እየዋለ እንዳልሆነ የማረጋገጥ ሃላፊነት አለባቸው።” 
“‘ሞትን  እዚሁ  መጠበቅ’፡ የግዳጅ ማፈናቀልና  ሰፈራ  በኢትዮጵያ  የጋምቤላ ክልል”  በ         http://www.hrw.org/reports/2012/01/17/waiting-here-death-0 ይገኛል።






  


0 comments:

Related Posts Plugin for WordPress, Blogger...