10 Jan 2017
አዲስ አበባ ጥር 1/2009 አገር በቀል መንግሥታዊ ያልሆነ የሴቶች ስትራቴጂካዊ ማዕከል ነገ በይፋ ሥራውን ይጀምራል።
የማዕከሉ መሥራችና ሥራ አስኪያጅ አምባሳደር ገነት ዘውዴ ለኢዜአ እንደገለጹት ማዕከሉ ሲቋቋም አራት ዋና ዋና ዓላማዎችን ታሳቢ አድርጎ ነው።
እንደ አምባሳደሯ ገለፃ ማዕከሉ የተለያዩ ምርምሮችን በማድረግ የምርምር ውጤቶችን ለመንግሥት የማቅረብና የሴቶችን የመምራት አቅም ለማሳደግ ታስቦ የተቋቋመ ነው።
በተጨማሪም “ሴቶች አይችሉም” የሚለውን የተዛባ አመለካከት ለመለወጥ ግንዛቤ የመፍጠሪያ መርሃ-ግብሮች ማዘጋጀትና ይህንኑ አስመልክቶ በየሦስት ወሩ መጽሄቶች እንደሚያዘጋጁ አምባሳደር ገነት ገልጸዋል።
አዳዲስ የሚወጡ የቴክኖሎጂ ውጤቶችና የሴቶችን የኑሮ ጫና በሚቀንሱ ጉዳዮች ላይም ማዕከሉ የሚሰራ ይሆናል።
ማዕከሉ የተቋቋመው በሲቪል ሰርቪስ ዩኒቨርሲቲ ግቢ ውስጥ ሲሆን ነገ ከሰዓት በኋላ ማዕከሉን አስመልክቶ መርሃ ግብር ተዘጋጅቷል።
